የበይነ መረብ መገናኛ ብዙሐን ፕሮፋይል / MIRH/ 05 ሀምሌ 2014
በመቅደስ ደምስ
ድሬ ቲዩብ በኢትዮጵያውያን የበይነመረብ ተደራስያን ዘንድ በሰፊው የሚታወቅና በኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሀን ባልስጣን የተመዘገበ የዩቲዩብ የመረጃ ምንጭ ነው፡፡ የመረጃ ምንጩ ወቅታዊ ዜና ዘገባዎችን በተንቀሳቃሽ ምስሎች በማጋራት ከጥቅምት ወር 2000 ጀምሮ በስርጭት ላይ ይገኛል፡፡ በቢኒያም ነገሱ የተጀመረው ድሬ ቲዩብ ተመልካቾች የተለያዩ ተንቀሳቃሽ ምስሎችን የሚመለከቱበት፣ የሚያጋሩበትና የሚጭኑበት እንዲሁም አውርደው የሚጠቀሙበት የመረጃ ምንጭ ነው፡፡ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በአገር ውስጥና ከአገር ውጪ ላሉ ኢትዮጵያውን ቀዳሚው የበይነመረብ መረጃና መዝናኛ ምንጭ ለመሆን በቅቷል፡፡
የመረጃ ምንጩ ስያሜውን ያገኘው ከድሬደዋ ከተማ ስም ነው፡፡ ድሬ ማለት በኦሮምኛ ቋንቋ ቦታ ወይም ስፍራ ማለት ነው፡፡ ስያሜውም ድሬ ትዩብ የተንቀሳቃሽ ምስሎችና የመረጃ መገኛ ቦታ መሆኑን ያመለክታል፡፡
DireTube.com እና የድሬ ቲዩብ ፌስቡክ ገጽ ባለቤትነት የሆቢ ኔት ሚዲያ ሓላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር (Hobinet Media PLC) ሲሆን ተቀማጭነቱ አዲስ አበባ ነው፡፡ የድሬ ቲዩብ ፌስ ቡክ ገጽ ከ3 ነጥብ 1 ሚሊዮን በላይ ተከታዮች ያለው ሲሆን አዲስ አበባ ከሚገኝ ዋናው ቢሮው በተጨማሪ በድሬደዋ ተጨማሪ ቅርንጫፍ ቢሮ አለው፡፡
በድሬ ቲዩብ ላይ የሚቀርቡ ድራማዎች፣ ዜናና አዝናኛ ተንቀሳቃሽ ምስሎች ምንጮች ፊልም ሰሪ ድርጅቶች፣ ከድሬ ቲዩብ ጋር ግንኙነት ያላቸው የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙሀን ተቋማት እና የራሱ የድሬ ቲዩብ ሠራተኞች ናቸው፡፡
“ድሬ ቲዩብ ህግ”፣ “ድሬ ቲዩብ ጤና”፣ “ድሬ ቲዩብ የወንጀል ታሪክ”፣ “ድሬ ቲዩብ ዘጋቢ ፊልም” እና “ድሬ ቲዩብ ግጥም” ከድሬ ቲዩብ ዝግጅቶች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
አሁን ላይ በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በተመለከተ ስለአገራቸው በቂ መረጃ እንዲያገኙ ሰፊ ሥራን እየሰራ ይገኛል፡፡ ይህን ተግባሩንም በስፋት ለመቀጠል እቅድ አዘጋጅቶ በመስራት ላይ ነው፡፡ ድሬ ቲዩብ በድረ-ገጽ፣ ዩቲዩብ፣ ፌስቡክና ሌሎች ማህበራዊ መገናኛ ብዙሀን አማካኝነት ዝግጅቶቹን ለተከታዮቹ ያደርሳል፡፡ በአሁኑ ወቅት ሥራውን የሚያከናውነው በስምንት ቋሚና በአስር የትርፍ ጊዜ ሠራተኞቹ ነው፡፡
ምንጭ:
DireTube.com
የስልክ አድራሻ 011 470 1686
Comments