የምስል ወድምፅ ቅንብሮች / MIRH/ 30 መስከረም 2015
“የመገናኛ ብዙሃን የሰላም አዘጋገብ በኢትዮጵያ” ኹሉንም ባለድርሻ አካላት ያሳተፈ ውይይት ተካሄደ፡፡
የኢትዮጵያ ናሽናል ሚዲያ ሳፖርት እና አይ ኤም ኤስ ፕራይምድ (IMS – PRIMED) “የመገናኛ ብዙሃን የሰላም አዘጋገብ በኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ በትብብር ያዘጋጁት የባለድርሻ አካላት ውይይት መስከረም 26, 2015 ዓ.ም በአዲስ አበባ አዜማን ሄቴል ተካሂዷል፡፡
መድረኩ በራሽዊት ሙኩንዱ በአይ ኤም ኤስ (IMS-PRIMED ENMS) ከሠሃራ በታች ያሉ የአፍሪቃ ሀገራት አማካሪ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር የተጀመረ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ ብሮድካስት አሰራጮች ማኅበር ሥራ አስኪያጅ እንዳሻው ወ/ሚካኤል (ዶ/ር) የእለቱን ዝግጅት አስመልክቶ እጅግ ጠቃሚ የሆነ መልእክት ለተሳታፊዎች አስተላልፈዋል፡፡
በኢትዮጵያ ያለው የእርስ በእርስ ጦርነት፣ ብሔር ተኮር ግጭቶች፣ ሞት እና መፈናቀል እንዲቆም እና በሁሉም ወገኖች ያሉ አካላት ስለሰላም እንዲሰብኩ የመገናኛ ብዙሃን ሚና ላይ ትኩረት ያደረገ ጥናታዊ ጽሑፍ በተባባሪ ፕሮፌሰር ተሻገር ሽፈራው (ደ/ር) ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቀርቧል፡፡ በተጨማሪም ሦስት የሚዲያ ባለሙያዎች በቀረበው ጥናታዊ ጽሁፍ ላይ ለውይይት መነሻ የሆኑ ልዩ ልዩ ርዕሰ ጉዳዮችን አቅርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
በውይይቱ ላይ የሚዲያ አካላት፣ ማኅበራት፣ ጋዜጠኝነት ትምህርት ቤት (ዩኒቨርሲቲዎች) የመጡ ግለሰቦች፣ የማኅበሰብ ሬዲዮ ተወካዮች፣ ጋዜጠኞች፣ ኤምባሲዎች እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተው ገንቢ ውይይት ተደርጓል፡፡
የአገራችን መገናኛ ብዙሃን ከሰላም ግንባታ አንጻር ሊኖራቸው ስለሚገባው ሚና ተግባራዊ ይሆን ዘንድ የአቅም ግንባታ ሥራ በሰፊው መሠራት እንዳለበት ተወያዮች በስፋት አንስተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ናሽናል ሚዲያ ሳፖርት (ENMS) ዳይሬክተርና የፕሮግራም ክፍል ኀላፊ አቶ ፍቃዱ አለሙ መዝጊያ ንግግር በማድረግ የጉባኤውን ሀሳብ አጠቃለዋል፡፡ በተጨማሪም የመገናኛ ብዙኀን የሰላም አዘጋገብ አገራችን አሁን ላለችበት ሁኔታ ትልቅ አስተዋጽኦ ያለው በመሆኑ ብዙ ሊሰራበት እንደሚገባ ተመላክቷል፡፡
Comments